አዲስ አበባ

Ethiopia / Addis Abeba /
 ከተማ, ዋና ከተማ, የአገር ዋና ከተማ

እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር፣ በ1879 ዓመተ ምሕረት የተመሰረተችው አዲስ አበባ፣ የኢትዮጵያ ዋና ከተማ ስትሆን፣ በተጨማሪም፣ አፍሪቃን የሚመለከቱ ዓለም አቀፋዊ ጉዳዮች የሚስተናገዱባት አሕጉራዊ ማዕከል ናት። ከ5,000,000 በላይ እንደሚሆን በሚገመተው የሕዝብ በዛትና፣ መጠነ ሰፊ በሆነው የከተማ ቦታ ይዞታዋ አንፃር ሲታይ፣ አዲስ አበባ በሀገሪቱ ውስጥ ወደር የሌላት ትልቋ ከተማ ናት። በአቀማመጥ፣ ምንም እንኳን ከምድር መቀነት ቀረብ ያለ ቦታ ላይ ያለች ብትሆንም፣ አዲስ አበባ ከባሕር ጠለል ከ2,100 እስከ 2,700 ሜትር (6,900 እስከ 8,860 ጫማ) በሚደርስ ከፍ ያለ ቦታ ላይ የምትገኝ በመሆንዋ፣ ምቹ የሆነ የአየር ፀባይ ያላት ከተማ ነች።

በ1879 ዓመተ ምሕረት፣ እቴጌ ጣይቱ ብጡል ከባለቤታቸው ከዳግማዊ ምኒልክ ጋር በመተባበር፣ ደጋማውን እንጦጦ በመተው፣ ከተራራው በስተደቡብ በኩል ዝቅ ብሎ ከሚገኝው ፍልውኃ አካባቢ አዲስ ሰፈር መሰረቱ። ከአካባቢውም ተፈጥሮአዊ ውበት በመነሳሳት፣ እቴጌ ጣይቱ፣ አዲሱን የሰፈራ ቦታ ሰም አወጡለት፤ አዲስ አበባ ብለው ጠሩት።

አንፃራዊ በሆነ መንገድ ሲታይ፣ አዲስ አበባ ከተመሰረተችበት ከአንድ ምእተ ዓመት ትንሽ ብቻ ላቅ ባለ ጊዜ ውስጥ፣ ብዙ ደረጃዎችን ፈጥና በመሸጋገር፣ አፍሪቃ ውስጥ ካሉት አንጋፋ ከተማዎች ጎን በአቻነት ለመሰለፍ በቅታለች።

አዲስ አበባ፣ የአፍሪቃ አንድነት (በእንግሊዝኛ ምሕፃረ ቃል፣ ኤዩ በመባል የሚታወቀው) ዋና መሥሪያ ቤት፣ እንዲሁም፣ የተባበሩት መንግሥታት ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ለአፍሪቃ (ኢሲኤ) ዋና መሥሪያ ቤት ይገኙባታል። ስለሆነም፣ ከተማዋ ብዛት ያላቸው የዓለም አቀፍ የዲፕሎማሲ ልኡካን የሚስተናገዱባትና፣ ከዚሁም ውስጥ የ95 አገር ኤምባሲዎች የሚገኙባት ናት።
ቀረብ ያሉ ከተማዎች:
መጋጠሚያ፥   8°57'57"N   38°46'14"E

አስተያየቶች